ኡሁሩ ኬንያታ በሰላም ንግግሩ ውስጥ እንደማይሳተፉ አሳወቁ

በሰሜን ኢትዮጵያ ያለውን ጦርነት ለማብቃት ለሚደረገው ጥረት በአፍሪካ ኅብረት ከተሰየሙት አሸማጋዮች መካከል አንዱ የሆኑት የቀድሞው የኬንያ ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ በንግግሩ ውስጥ እንደማይሳተፉ አሳወቁ።

በኢትዮጵያ መንግሥት እና በትግራይ ኃይሎች መካከል ንግግር እንዲጀመር የአፍሪካ ኅብረት ባቀረበው ጥሪ መሠረት በሳምንቱ ማብቂያ ላይ ደቡብ አፍሪካ ውስጥ ውይይት ይካሄዳል ተብሎ እየተጠበቀ ነበር።

ከአፍሪካ ኅብረት የአፍሪካ ቀንድ ከፍተኛ ተወካይ ኦሉሴጎን ኦባሳንጆ፣ ከደቡብ አፍሪካ ምክትል ፕሬዝዳንት ዶ/ር ፉምዚሌ ምላምቦ-ናግኩካ ጋር በአሸማጋይነት በንግግሩ ይሳተፋሉ ተብለው የነበሩት ኬንያታ በመጨረሻው ሰዓት ነው እራሳቸውን ያገለሉት።