አንቶኒ ብሊንከን ስለሰላም ንግግሩ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ጋር መነጋገራቸው ተገለጸ

የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን በፌደራል መንግሥቱ እና በትግራይ ኃይሎች መካከል በደቡብ አፍሪካ እየተካሄደ ስላለው የሰላም ውይይት በተመለከተ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ጋር መነጋገራቸውን ገለጹ።

የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ትናንት ጥቅምት 15/2015 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ፤ ብሊንከን ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ጋር የተነጋገሩት ግጭቱ በአስቸኳይ ማቆምን በተመለከተ ነው።

ከዚህም በተጨማሪ ብሊንከን በዚሁ ጉዳይ ላይ ከኬንያው ፕሬዝደንት ዊሊያም ሩቶ እና ከደቡብ አፍሪካው የዓለም አቀፍ ግንኙነት እና ትብብር ሚኒስትር ፓንዶር ጋር መነጋገራቸውን ገልጸዋል።

“ግጭቱ ፖለቲካዊ መፍትሔ እንዲያገኝም ከአፍሪካ ኅብረት ጋር መምከሬን እቀጥላለሁም ብለዋል” የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በመግለጫቸው።