የአሜሪካው ልዩ መልዕክተኛ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ጋር መነጋገራቸው ተገለጸ  

በአፍሪካ ቀንድ የአሜሪካ መንግሥት ልዩ መልዕክተኛ የሆኑት አምባሳደር ማይክ ሐመር በኢትዮጵያ በነበራቸው ቆይታ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እና ከአገሪቱ ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጋር መገናኘታቸው ተገለጸ።

ለወራት ጋብ ብሎ የነበረው በሰሜን ኢትዮጵያ የሚካሄደው ጦርነት መልሶ ከተቀሰቀሰ በኋላ ወደ አፍሪካ ቀንድ በመምጣት ለቀናት የቆዩት ልዩ ልዑኩ በዋናነት ጦርነት ቆሞ ሁለቱም ወገኖች ድርድር እንዲጀምሩ ግፊት ሲያደርጉ መቆየታቸው ተነግሯል።

ነሐሴ 30/2014 ዓ.ም. አዲስ አበባ የገቡት አምባሳደር ሐመር አስከ መስከረም 05/2015 ዓ.ም. ድረስ በነበራቸው ቆይታ ዋነኛ አጀንዳቸው የነበረው የሰሜን ኢትዮጵያው የእርስ በርስ ጦርነት እንደነበር የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ያወጣው መግለጫ አመልክቷል።  

ልዩ መልዕክተኛው በአዲስ አበባ የአሜሪካ ኤምባሲ ጉዳይ ፈጻሚ ከሆኑት ትሬሲ አን ጃኮብሰን ጋር በመሆን ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እና ከምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ጋር ተገናኝተው መወያየታቸው ተገልጿል። (ምንጭ ቢቢሲ)