አሜሪካ ልዩ መልክተኛ ሾመች

አሜሪካ በኢትዮጵያና በአካባቢዋ ባሉ አገራት ውስጥ ስላሉ ጉዳዮች በቅርበት የሚከታተሉላትን ልዩ መልዕክተኛ መሾሟን የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት አስታወቀ።

የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን ይፋ እንዳደረጉት በተለይ ኢትዮጵያ ለምትገኝበት የአፍሪካ ቀንድ አካባቢ ጄፍሪ ፌልትማንን የአሜሪካ ልዩ መልዕክተኛ አድርገው መሾማቸውን ገልጸዋል።

አሜሪካ አዲስ የሾመቻቸው የአፍሪካ ቀንድ መልዕክተኛ ጄፍሪ ፌልትማን በተለይ በኢትዮጵያና በዙሪያዋ ስላሉ ሁኔታዎች የተለየ ትኩረት እንደሚሰጡ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤቱ አመልክቷል።

በዚህም መሠረት በኢትዮጵያ ሰሜናዊ ክፍል ትግራይ ክልል ውስጥ ያለውን ግጭት ጨምሮ በአገሪቱ ያለው ተለዋወጭ ሁኔታ፣ ከሱዳን ጋር ያለውን የድንበር አለመግባባት እንዲሁም በታላቁ የሕዳሴ ግድብ ዙሪያ ያለው ውዝግብ የልዩ ልዑኩ ቀዳሚ ሥራ እንደሚሆን ተገልጿል።