የፌዴሬሽን ምክር ቤት በትግራይ ክልል መንግሥት ላይ ውሳኔ አሳለፈ

የፌዴራል መንግሥት ከትግራይ ክልል መንግሥት ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት እንዳያደርግ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ውሳኔ አሳለፈ፡፡

ምክር ቤቱ ውሳኔውን ያሳለፈው ነሐሴ 30 ቀን 2012 ዓ.ም. አድርጎት በነበረው አስቸኳይ ጉባዔ፣ በትግራይ ክልል የሚካሄደው ምርጫ እንዳልተደረገና እንደማይፀና ያስተላለፈው ውሳኔ ተጥሶ በማግኘቱ መሆኑን ትናንት ማምሻውን በመንግሥት መገናኛ ብዙኃን አሳውቋል፡፡

ምክር ቤቱ ያስተላለፈውን ውሳኔ ሲከታተል የነበረው የሕገ መንግሥት ጉዳዮችና የማንነት ጉዳዮች አጣሪ ኮሚቴ፣ ክልሉ የፌዴሬሽኑን ውሳኔ ባለማክበሩና ባለመፈጸሙ፣ ትናንት መስከረም 26 ቀን 2013 ዓ.ም. ባደረገው መደበኛ ስብሰባው፣ የፌዴራል መንግሥት ከትግራይ ክልል መንግሥት ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት እንዳያደርግ ውሳኔ ማሳለፉን ኢቢሲ ዘግቧል፡፡

ምክር ቤቱ በትግራይ ክልል መንግሥት ላይ ሦስት ውሳኔዎችን ማሳለፉን የገለጸ ሲሆን፣ የመጀመርያው ክልሉ ያካሄደውን ኢሕገ መንግሥታዊ ምርጫን ተከትሎ ከተመሠረቱ፣ የትግራይ ክልል ምክር ቤትና ከፍተኛ የሕግ አስፈጻሚ አካላት ጋር፣ የፌዴራል መንግሥት ምንም ዓይነት ግንኙነት አያደርግም፡፡ ሁለተኛው ውሳኔ ደግሞ የፌዴራል መንግሥት የትግራይ ሕዝብን የልማትና መሠረታዊ አገልግሎቶች ፍላጎትን ማዕከል በማድረግ፣ የከተማና የቀበሌ አስተዳደርን ጨምሮ፣ በክልሉ ከሚገኙ ሕጋዊ ተቋማት ጋር ብቻ የሥራ ግንኙነት እንደሚያደርግ ወስኗል፡፡ በመጨረሻም የውሳኔውን አፈጻጸም በፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔና ጉዳዩ በሚመለከታቸው ቋሚ ኮሚቴ ክትትል መደረግ እንዳለበትም ምክር ቤቱ ውሳኔ አሳልፏል፡፡

የፌዴሬሽን ምክር ቤት ትናንት መስከረም 26 ቀን 2013 ዓ.ም.፣ የ2013 ዓ.ም. መደበኛ ስብሰባውን ሲያካሂድ፣ ሪፖተር ጋዜጣን ጨምሮ የተለያዩ መገናኛ ብዙኃን የተገኙ ቢሆንም፣ ስብሰባው በዝግ እንደሚካሄድ ተነግሮ እንዳይገቡ ተከልክለዋል፡፡ ሆኖም ግን በዕለቱ አመሻሹ ላይ ምክር ቤቱ ከላይ የተገለጹትን ውሳኔዎች ማሳለፉን የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ዘግቧል፡፡