ህወሃትና መንግስት ልዮነታቸውን በድርድር እንዲፈቱ የፓለቲካ አመራሮች ጠየቁ

የህወኃት አመራሮች እየፈጸሙት ያለው ህገ-ወጥ ድርጊት ካላቸውን ረጅም የፖለቲካ ልምድ አኳያ ተገቢ አለመሆኑን ኢዜአ ያነጋገራቸው ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ገለጹ።

ለትግራይ ህዝብ ክብርና ጥቅም ሲባል የፌዴራል መንግስትና የህወኃት አመራሮች በድርድር ችግራቸውን ሊፈቱ ይገባልም ነው ያሉት።

በኢፌዴሪ ህገ- መንግስት አንቀፅ 102 ንኡስ ቁጥር 1 መሰረት በፌዴራልም ሆነ በክልሎች የሚደረጉ ምርጫዎችን የማስፈፀም ስልጣን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ መሆኑ በግልጽ ተቀምጧል።

በኢትዮጵያ ወረርሽኙ መከሰቱ እንደታወቀ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ከሚመለከታቸው ባለደርሻ አካላት ጋር በመካከር ቦርዱ ቀደም ሲል ባወጣው የምርጫ የጊዜ ሰሌዳ መሰረት ማካሄድ የማይችል መሆኑን አሳውቋል።

ይሁንና በትግራይ ክልል ከኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ዕውቅና ውጭ ጳጉሜን 4 ቀን 2012 ዓ.ም ክልላዊ ምርጫ ተካሂዷል።

ምርጫው የትግራይ ክልልን እያስተዳደረ ያለው የህወኃት አመራሮች ህገ ወጥ ድርጊት መሆኑን ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ተናግረዋል።

የህወኃት አመራሮች እየፈጸሙት ያለው ህገ-ወጥ ድርጊት ካላቸው የረጅም ጊዜ የፖለቲካ ልምድ አኳያ ተገቢ አለመሆኑን ገልጸዋል።