መፍትሄው ዲፕሎማሲ ብቻ ነው – አሜሪካ

የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት የቀጠናዊ ጉዳዮች ቃል አቀባይ ሳሙኤል ዋርበርግ፤ ትላንት እሁድ በሰጡት ቃል አሜሪካ ለታላቁ የኢትዮጵያ የህዳሴው ግድብ ጉዳይ ብቸኛው መፍትሄ ዲፕሎማሲ ነው ብላ ታምናለች ብለዋል።

ከTeN የሳተላይት ቻናል ቃለምልልስ የነበራቸው ዋርበርግ ፥ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ፀጥታው ምክር ቤት ስብሰባ የህዳሴው ግድብ ጉዳይ ለአፍሪካ አህጉር እጅግ በጣም አስፈላጊ መሆኑን አሳይቷል ሲሉ ተናግረዋል።

አክለውም ዓላም አቀፉ ማህበረሰብ የህዳሴው ግድይ ጉዳይ ለናልይ ተፋሰስ ቀጠና ምን ያህል ጠቃሚ እንደሆነ ተገንዝቧል ብለዋል።

ዋርበርግ፥ የግድቡ ጉዳይ ምንም አይነት ወታደራዊ መፍትሄ እንደሌለው በማንሳት “በአፍሪካ አህጉር ምንም አዲስ ጦርነት ልንገምት አንችልም” ብለዋል።

የተፋሰሱ አገራት እና የ አፍሪካ ህብረት ድርድርን እንደገና መጀመር እንዳለባቸው ጠቁመው አሜሪካ ማንኛውንም የፖለቲካ ወይም የቴክኒክ ድጋፍ ለመስጠት ዝግጁ መሆኗን ገልፀዋል።

ዋርበርግ፥ “ውይይቱን ለመቀጠል አሜሪካ ሁሉም ወገኖች ከማንኛውም መግለጫ እንዲታቀቡ ጥሪ ታደርጋለች ፤ የሚደረገው ማንኛውም ውይይት ድርድሮችን ወደፊት ለማስቀጠል ያለመ መሆን ይገባዋል” ብለዋል።

አሜሪካ ድርድሩ ላይ የበለጠ ጊዜ እንዲያልፍ አትፈልግም ብለዋል።